loading
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለዋና መስሪያ ቤትነት በአዲስ አበባ እያስገነባው የሚገኘውን ህንፃ ከ46 ወለል ወደ 48 ወለል ከፍ አደረገ

አርትስ 23/02/2011

ባንኩ የዋና መስሪያ ቤቱ ግንባታ የወለል ከፍታ እንዲጨምር ያደረገው ቀድሞ በነበረው ባለ 46 የወለል ከፍታ ዲዛይን ላይ ማሻሻያ በማድረግ ነው፡፡

እስከ 2012 ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ ይጠናቀቃል ተብሎ የሚጠበቀው ህንፃው ከ200 ሜትር በላይ በሚሆነው ርዝመቱ ከምስራቅ አፍሪካ የሚወዳደረውየለም ተብሏል፡፡

ህንፃውን ሙሉ ለሙሉ ገንብቶ ለማጠናቀቅ ወደ 300 ሚሊዮን ዶላር የሚጠጋ ወጪ እንደሚፈጅም ነው ከባንኩ የተገኘው መረጃ የሚያመለክተው፡፡

በቻይና የመንግስት ግንባታ ኮርፖሬሽን በ150 ሺህ ሜትር ስኩዌር ቦታ ላይ እየተገነባ ያለው ይኸው የምስራቅ አፍሪካ ረጅሙ ህንፃ፤ በተጨማሪም 2 ባለ 5 ወለል የስብሰባ ማእከልና አጠቃላይ አገልግሎት ህንፃዎችን ያካተተ ነው፡፡

በዚሁ የህንፃ ግንባታ ከወለል በታች ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ የምድር ውስጥ ወለሎችንም ያቀፈ ነው፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ የንግድ ማእከል በሆነው የብሄራዊ ቲያትር አካባቢ እየተገነባ የሚገኘው ህንፃው፤ በአራቱም ማዕዘናት ከተማዋን ፍንትው አድርጎየሚያሳይ ነው፡፡

ኢቢሲ  እንደዘገበዉ የህንፃው ግንባታ ሲጠናቀቅ በከተማዋ ውስጥ ከሚገኙ በቱሪስት ከሚጎበኙ ቦታዎች አንደኛው እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *