loading
ባልደራስ አመራሮቹን ከእስር ለማስፈታት ግፊት እንዲያደርጉ ለ15 አገሮች ጥሪ አቀረበ::

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 04፣ 2014 ባልደራስ አመራሮቹን ከእስር ለማስፈታት ግፊት እንዲያደርጉ ለ15 አገሮች ጥሪ አቀረበ:: ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) አቶ እስከንድር ነጋንና ሌሎች የፓርቲው አመራሮችን ከእስር የማስፈታት ግፊት እንዲያደርጉ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)ን ጨምሮ፣  ለ15 አገሮች ኤምባሲዎች ጥሪ ማቅረቡ ተገልጿል፡፡ የባልደራስ ፓርቲ የሕግ ጉዳዮች ኃላፊና የእነ አቶ አስክንድር ነጋ ጠበቃ አቶ ሔኖክ አክሊሉ ለሪፖርተር
እንዳስረዱት፣ በቀጣይ ደግሞ መንግሥታዊ ላልሆነው የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) ደብዳቤ ለማስገባት እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

ፓርቲው በመግለጫው እንዳስታወቀው መንግሥት በአትዮጵያ ውስጥ ያለውን የፍትሕ ሁኔታ ለማስተካከል ሚና ይጫወታል ብሎ ቢጠብቅም፣ ምንም ማድረግ አልቻለም ብሏል፡፡ ለአብነት ያህልም የፓርቲው አመራር በሆኑት አቶ እስከንድር ነጋ፣ አቶ ስንታየሁ ቸኮል፣ ወ/ሮ አስቴር ሥዩምና ወ/ሮ አስካለ ደምሌ ላይ የተደረገው ሕግን የተላለፈ እስር አንዱ ጉዳይ እንደሆነ አስታውቋል፡፡ ፓርቲው ለ15 አገሮች ኤምባሲዎችና ለኢሰመኮ ያቀረበው ጥሪ ዋነኛ ይዘት፣ የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ አመራር የሆኑት አቶ እስክንድር ነጋ ለረዥም ጊዜ ፍትሕ ሳያገኙ ስለመቆየታቸው መሆኑን የጠቆሙት አቶ ሔኖክ፣ ይህም ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ ለሕዝቡ ቃል ከገቡት የወጣ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ አቶ እስከንድር ታስረው የሚገኙት በፖለቲካ አቋማቸው በመሆኑ የህሊና እስረኛ መሆናቸውን፣ አጋር አካላትና የኢትዮጵያ ወዳጅ አገሮች ከመንግሥት ጋር ባላቸው ግንኙነት ተፅዕኖ በመፍጠር ከእሳቸው ጋር ያላግባብ የታሰሩት ሌሎች አመራሮች ከእስር ወጥተው ሰላማዊ የፖለቲካ
ሕይወታቸውን እንዲቀጥሉ የሚል ይዘት ያለው እንደሆነ አቶ ሔኖክ ጠቁመዋል፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *